ሆሴዕ 14

በረከትን ለማግኘት ንስሓ መግባት

1 እስራኤል ሆይ፤ በኀጢአትህ ምክንያት ስለ ወደቅህ፣

ወደ አምላክህ ወደእግዚአብሔርተመለስ።

2 የምትሉትን ቃል ይዛችሁ፣

ወደእግዚአብሔርተመለሱ፤

እንዲህም በሉት፤

“ኀጢአታችንን ሁሉ ይቅር በለን፤

የከንፈራችንንም ፍሬ እንድናቀርብ፣

በምሕረትህ ተቀበለን።

3 አሦር ሊያድነን አይችልም፤

በጦር ፈረሶችም ላይ አንቀመጥም፤

ከእንግዲህም የገዛ እጆቻችን የሠሯቸውን፣

‘አምላኮቻችን’ አንላቸውም፤

ድኻ አደጉ ከአንተ ርኅራኄ ያገኛልና።”

4 “እኔ ከዳተኛነታቸውን እፈውሳለሁ፤

እንዲሁ እወዳቸዋለሁ፤

ቊጣዬ ከእነርሱ ተመልሶአልና።

5 እኔ ለእስራኤል እንደ ጠል እሆናለሁ፤

እንደ ውብ አበባ ያብባል፤

እንደ ሊባኖስ ዝግባም፣

ሥር ይሰዳል፤

6 ቅርንጫፉ ያድጋል፤

ውበቱ እንደ ወይራ ዛፍ፣

ሽታውም እንደ ሊባኖስ ዝግባ ይሆናል።

7 ሰዎች እንደ ገና ከጥላው በታች ያርፋሉ፤

እርሱም እንደ እህል ይለመልማል፤

እንደ ወይን ተክል ያብባል፤

ዝናውም እንደ ሊባኖስ የወይን ጠጅ ይወጣል።

8 ኤፍሬም ሆይ፤ ከእንግዲህ ከጣዖት ጋር

ምን ጒዳይ አለኝ?

የምሰማህና የምጠነቀቅልህ እኔ ነኝ፤

እኔ እንደለመለመ የጥድ ዛፍ ነኝ፤

ፍሬያማነትህም ከእኔ የተነሣ ነው።”

9 ጥበበኛ የሆነ እነዚህን ነገሮች ያስተውላል፤

አስተዋይም እነዚህን ነገሮች ይረዳል።

የእግዚአብሔርመንገድ ቅን ነውና፤

ጻድቃን ይሄዱበታል፤

ዐመፀኞች ግን ይሰናከሉበታል።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *