መዝሙር 101

ትክክለኛ አስተዳደር

የዳዊት መዝሙር

1 ስለ ምሕረትና ስለ ፍትሕ እዘምራለሁ፤

እግዚአብሔርሆይ፤ ለአንተ በምስጋና እቀኛለሁ።

2 እንከን የማይገኝባትን መንገድ አጥብቄ እይዛለሁ፤

አንተ ወደ እኔ የምትመጣው መቼ ነው?

በቤቴ ውስጥ፣

በንጹሕ ልብ እመላለሳለሁ።

3 በዐይኔ ፊት፣

ክፉ ነገር አላኖርም።

የከሓዲዎችን ሥራ እጠላለሁ፤

ከእኔም ጋር አይጣበቅም።

4 ጠማማ ልብ ከእኔ ይርቃል፤

ለክፋትም ዕውቅና አልሰጥም።

5 ባልንጀራውን በስውር የሚያማውን፣

አጠፋዋለሁ፤

ትዕቢተኛ ዐይንና ኵራተኛ ልብ ያለውን፣

እርሱን አልታገሠውም።

6 ከእኔ ጋር ይኖሩ ዘንድ፣

ዐይኖቼ በምድሪቱ ታማኞች ላይ ናቸው፤

በንጽሕና መንገድ የሚሄድ፣

እርሱ ያገለግለኛል።

7 አታላይ የሆነ ማንም ሰው፣

በቤቴ ውስጥ አይኖርም፤

ሐሰትን የሚናገር፣

በፊቴ ቀና ብሎ አይቆምም።

8 በምድሪቱ ላይ ያሉትን ክፉዎች ሁሉ፣

በየማለዳው አጠፋቸዋለሁ፤

ክፉ አድራጊዎችንም ሁሉ፣

ከእግዚአብሔርከተማ እደመስሳቸዋለሁ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *