መዝሙር 28

ልመናና ምስጋና

የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔርሆይ፤ ወደ አንተ እጣራለሁ፤

ዐለቴ ሆይ፤ ሰምተህ እንዳልሰማ አትሁንብኝ፤

አንተ ዝም ካልኸኝ፤

ወደ ጒድጓድ እንደሚወርዱ እሆናለሁ።

2 ለርዳታ በጮኽሁ ጊዜ፣

ወደ ቅዱስ ማደሪያህ፣

እጆቼን በዘረጋሁ ጊዜ፣

የልመናዬን ቃል ስማ።

3 በልባቸው ተንኰል እያለ፣

ከባልንጀሮቻቸው ጋር በሰላም ከሚናገሩ፣

ከክፉ አድራጊዎችና፣

ከዐመፃ ሰዎች ጋር ጐትተህ አትውሰደኝ።

4 እንደ ሥራቸው፣

እንደ ክፉ ተግባራቸው ክፈላቸው፤

እንደ እጃቸው ሥራ ስጣቸው፤

አጸፋውን መልስላቸው።

5 ለእግዚአብሔርሥራ ግድ ስለሌላቸው፣

ለእጆቹም ተግባራት ስፍራ ስላልሰጡ፣

እርሱ ያፈርሳቸዋል፤

መልሶም አይገነባቸውም።

6 የልመናዬን ቃል ሰምቶአልና፣

እግዚአብሔርየተባረከ ይሁን።

7 እግዚአብሔርብርታቴና ጋሻዬ ነው፤

ልቤ በእርሱ ይታመናል፤ እርሱም ዐግዞኛል፤

ልቤ ሐሤት አደረገ፤

በዝማሬም አመሰግነዋለሁ።

8 እግዚአብሔርለሕዝቡ ብርታታቸው ነው፤

ለቀባውም የመዳን ዐምባ ነው።

9 ሕዝብህን አድን፤ ርስትህንም ባርክ፤

እረኛ ሁናቸው፤ ለዘላለሙም ዐቅፈህ ያዛቸው።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *