መዝሙር 53

አምላክ የለሾች

ለመዘምራን አለቃ፤ በማኸላት፤ የዳዊት ትምህርት።

1 ቂል በልቡ፣

“እግዚአብሔር የለም” ይላል።

ብልሹዎች ናቸው፤ ተግባራቸውም ጸያፍ ነው፤

በጎ ነገርን የሚያደርግ አንድ እንኳ የለም።

2 በማስተዋል የሚመላለስ፣

እግዚአብሔርን የሚፈልግ እንዳለ ለማየት፣

እግዚአብሔር ከሰማይ፣

ወደ ሰው ልጆች ተመለከተ።

3 ሁሉም ወደ ሌላ ዘወር አሉ፤

በአንድነትም ተበላሹ፤

አንድ እንኳ፣

በጎ የሚያደርግ የለም።

4 ሰው እንጀራ እንደሚበላ ሕዝቤን የሚበሉት፣

እግዚአብሔርንም ጠርተው የማያውቁት፣

እነዚያ ክፉ አድራጊዎች ከቶ አይማሩምን?

5 የሚያስፈራ ነገር በሌለበት፣

በዚያ፣ በፍርሀት ተዋጡ፤

እግዚአብሔር የዘመቱብህን ሰዎች ዐጥንት በተነ፤

እርሱ እግዚአብሔር ስለ ናቃቸው፣ አንተ አሳፈርሃቸው።

6 ምነው ለእስራኤል የሚሆን መዳን ከጽዮን በወጣ!

እግዚአብሔር የሕዝቡን ምርኮ በሚመልስበት ጊዜ፣

ያዕቆብ ሐሤት ያድርግ፤ እስራኤል ደስ ይበለው።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *