መዝሙር 57

በጨካኝ ጠላቶች ዘንድ

ለመዘምራን አለቃ፤ “አታጥፋ” በሚለው ቅኝት የሚዘመር፤ ከሳኦል ፊት ሸሽቶ በዋሻ በነበረበት ጊዜ፤ የዳዊት ቅኔ።

1 ማረኝ፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ ማረኝ፤

ነፍሴ አንተን መጠጊያ አድርጋለችና፤

በክንፎችህ ሥር እጠለላለሁ።

2 ለእኔ ያሰበውን ወደሚፈጽምልኝ አምላክ፣

ወደ ልዑል እግዚአብሔር እጮኻለሁ።

3 ከሰማይ ልኮ ያድነኛል፤

የረገጡኝን ያዋርዳቸዋል፤ሴላ

እግዚአብሔር ምሕረቱንና ታማኝነቱን ይልካል።

4 ነፍሴ በአንበሶች ተከብባለች፤

በሚዘነጣጥሉ አራዊት መካከል ወድቄአለሁ፤

እነዚህም፣ ጥርሳቸው ጦርና ፍላጻ፣

ምላሳቸውም የተሳለ ሰይፍ የሆኑ ሰዎች ናቸው።

5 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከሰማያት በላይ ከፍ ከፍ በል፤

ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትስፈን።

6 ለእግሬ ወጥመድን ዘረጉ፤

ነፍሴንም አጐበጧት፤

በመተላለፊያዬ ላይ ጒድጓድ ቈፈሩ፤

ነገር ግን ራሳቸው ገቡበት።ሴላ

7 እግዚአብሔር ሆይ፤ ልቤ ጽኑ ነው፤

ልቤ ጽኑ ነው፤

እቀኛለሁ፤ አዜማለሁ።

8 ነፍሴ ሆይ፤ ንቂ!

በገናና መሰንቆም ተነሡ

እኔም በማለዳ እነሣለሁ።

9 ጌታ ሆይ፤ በሕዝቦች መካከል አመሰግንሃለሁ፤

በሰዎችም መካከል እዘምርልሃለሁ፤

10 ምሕረትህ እስከ ሰማያት ከፍ ብላለችና፤

ታማኝነትህም እስከ ደመናት ትደርሳለች።

11 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከሰማያት በላይ ከፍ ከፍ በል፤

ክብርህም በምድር ሁሉ ላይ ትስፈን።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *