መዝሙር 64

የተሳዳቢዎች ቅጣት

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር

1 አምላክ ሆይ፤ የብሶት ቃሌን ስማ፤

ሕይወቴንም ከሚያስፈራ የጠላት ዛቻ ከልላት።

2 ከክፉዎች አድማ ሰውረኝ፤

ከዐመፀኞችም ሸንጎ ጋርደኝ።

3 እነርሱ ምላሳቸውን እንደ ሰይፍ ይስላሉ፤

መርዘኛ ቃላቸውንም እንደ ፍላጻ ያነጣጥራሉ።

4 አሸምቀው ንጹሑን ሰው ይነድፉታል፤

ድንገት ይነድፉታል፤ አይፈሩምም።

5 ክፉ ተግባር ለማከናወን እርስ በርስ ይመካከራሉ፤

በስውር ወጥመድ ለመዘርጋት ይነጋገራሉ፤

“ማንስ ሊያየን ይችላል?”ይባባላሉ።

6 ግፍን ያውጠነጥናሉ፤

ደግሞም፣ “የረቀቀች ሤራ አዘጋጅተናል” ይላሉ፤

አቤት! ልቡ፣ አእምሮውም እንዴት ጥልቅ ነው!

7 እግዚአብሔር ግን በፍላጻው ይነድፋቸዋል፤

እነርሱም ድንገት ይቈስላሉ።

8 በገዛ ምላሳቸው ያሰናክላቸዋል፤

ጥፋትንም ያመጣባቸዋል፤

የሚያዩአቸውም ሁሉ በትዝብት ራሳቸውን ይነቀንቃሉ።

9 የሰው ልጆች ሁሉ ይፈራሉ፤

የእግዚአብሔርን ሥራ በይፋ ያወራሉ፤

ያደረገውንም በጥሞና ያሰላስላሉ።

10 ጻድቅበእግዚአብሔርደስ ይበለው፤

እርሱንም መጠጊያ ያድርገው፤

ልበ ቅኖችም ሁሉ ደስ ይበላቸው።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *