መዝሙር 67

የመከር ጊዜ መዝሙር

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች የሚዘመር፤ የዳዊት መዝሙር፤ ማኅሌት

1 እግዚአብሔር ይማረን፤ ይባርከን፤

ፊቱንም በላያችን ያብራ፤ሴላ

2 መንገድህ በምድር ላይ፣

ማዳንህም በሕዝቦች ሁሉ መካከል ይታወቅ ዘንድ።

3 እግዚአብሔር ሆይ፤ ሰዎች ያመስግኑህ፤

ሰዎች ሁሉ ምስጋና ያቅርቡልህ።

4 ለሕዝቦች በቅን ስለምትፈርድላቸው፣

ሰዎችንም በምድር ላይ ስለምትመራ፣

ሕዝቦች ደስ ይበላቸው፤ በእልልታም ይዘምሩ።ሴላ

5 እግዚአብሔር ሆይ፤ ሰዎች ያመስግኑህ፤

ሰዎች ሁሉ ምስጋና ያቅርቡልህ።

6 ምድር ፍሬዋን ሰጠች፤

እግዚአብሔር አምላካችንም ይባርከናል።

7 እግዚአብሔር ይባርከናል፤

የምድርም ዳርቻዎች ሁሉ እርሱን ይፈሩታል።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *