ራእይ 15

ሰባቱ መላእክትና ሰባቱ መቅሠፍቶች

1 ሌላም ታላቅና አስደናቂ ምልክት በሰማይ አየሁ፤ የመጨረሻዎቹን ሰባት መቅሠፍቶች የያዙ ሰባት መላእክት አየሁ፤ የመጨረሻ የተባሉትም የእግዚአብሔር ቊጣ የሚፈጸመው በእርሱ በመሆኑ ነው።

2 ከእሳት ጋር የተቀላቀለ የብርጭቆ ባሕር የሚመስል አየሁ፤ በባሕሩም አጠገብ አውሬውን፣ ምስሉንና የስሙን ቊጥር ድል የነሡትን ቆመው አየሁ፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን በገና ይዘው፣

3 የእግዚአብሔር ባሪያ የሆነውን የሙሴን መዝሙርና የበጉን መዝሙር እንዲህ እያሉ ይዘምሩ ነበር፤

“ሁሉን ቻይ ጌታ አምላክ ሆይ፤

ሥራህ ታላቅና አስደናቂ ነው።

የዘመናትንጉሥ ሆይ፤

መንገድህ ጽድቅና እውነት ነው።

4 ጌታ ሆይ፤ አንተን የማይፈራ፣

ስምህን የማያከብርስ ማን ነው?

አንተ ብቻ ቅዱስ ነህና።

የጽድቅ ሥራህ ስለ ተገለጠ፣

ሕዝቦች ሁሉ ይመጣሉ፤

በፊትህም ይሰግዳሉ።

5 ከዚህ በኋላም አየሁ፤ በሰማይ ያለው ቤተ መቅደስ፣ ይኸውም የምስክሩ ድንኳን ተከፍቶ ነበር፤

6 ሰባቱን መቅሠፍቶች የያዙት ሰባቱ መላእክት ከቤተ መቅደሱ ወጡ፤ እነርሱም ከተልባ እግር የተሠራ ንጹሕ የሚያበራ ልብስ ለብሰው፣ ደረታቸውንም በወርቅ መታጠቂያ ታጥቀው ነበር።

7 ከዚያም ከአራቱ ሕያዋን ፍጡራን አንዱ ከዘላለም እስከ ዘላለም በሚኖረው አምላክ ቊጣ የተሞሉትን ሰባት የወርቅ ጽዋዎች ለሰባቱ መላእክት ሰጣቸው።

8 ቤተ መቅደሱም ከእግዚአብሔር ክብር፣ ከኀይሉም በወጣው ጢስ ተሞላ፤ የሰባቱ መላእክት ሰባት መቅሠፍቶች እስኪፈጸሙ ድረስ ማንም ወደ ቤተ መቅደሱ መግባት አልቻለም።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *