ኤርምያስ 6

የኢየሩሳሌም መከበብ

1 “እናንት የብንያም ልጆች፤ ክፉ ነገር፣

ታላቅም ጥፋት ከሰሜን ድንገት ይመጣልና፣

ከኢየሩሳሌም ሸሽታችሁ አምልጡ፤

በቴቁሔ መለከትን ንፉ፤

በቤትሐካሪም ላይ ምልክት ከፍ

አድርጋችሁ አሳዩ።

2 ውብና ሽሙንሙን የሆነችዋን፣

የጽዮንን ሴት ልጅ አጠፋታለሁ።

3 እረኞች መንጎቻቸውን ይዘው ይመጡባታል፤

ድንኳናቸውን በዙሪያዋ ይተክላሉ፤

እያንዳንዳቸውም በየአቅጣጫቸው መንጋቸውን ያሰማራሉ።”

4 “በእርሷ ላይ ጦርነት ዐውጁ፤

ተነሡ በቀትር አደጋ እንጣልባት፤

ወይ ጉድ! ቀኑ እኮ መሸብን!

ጥላው ረዘመ።

5 እንግዲህ ተነሡ በሌሊት እናጥቃት፤

ምሽጎቿንም እንደምስስ!”

6 የሰራዊት ጌታእግዚአብሔርእንዲህ ይላል፤

“ዛፎቹን ቍረጡ፤

በኢየሩሳሌም ዙሪያ የዐፈር ድልድል ሥሩ።

ይህቺ ከተማ ቅጣት ይገባታል፤

ግፍን ተሞልታለችና።

7 የውሃ ጒድጓድ ውሃ እንደሚያመነጭ፣

እርሷም እንዲሁ ክፋቷን ታፈልቃለች።

ዐመፅና ጥፋት በውስጧ ይስተጋባል፤

ሕመሟና ቍስሏ ዘወትር ይታየኛል።

8 ኢየሩሳሌም ሆይ፤ ተጠንቀቂ፤

አለበለዚያ ከአንቺ ዘወር እላለሁ፤

ማንም ሊኖርባት እስከማይችል ድረስ፣

ምድርሽን ባዶ አደርጋለሁ።”

9 የሰራዊት ጌታእግዚአብሔርእንዲህ ይላል፤

“የወይን ፍሬ ተሟጦ እንደሚቃረም፣

ከእስራኤል የተረፉትን እንዲሁ ይቃርሟቸው።

ወይን ለቃሚ እንደሚለቅም፣

እጅህን ወደ ቅርንጫፎቹ ደጋግመህ ዘርጋ።”

10 ለማን ልናገር? ማንን ላስጠንቅቅ?

ማንስ ይሰማኛል?

እነሆ፣ ጆሮዎቻቸው አልተገረዙምና፣

መስማት አይችሉም።

በእግዚአብሔርቃል ይሣለቃሉ፤

ደስም አይሰኙበትም።

11 በእነርሱ ላይበእግዚአብሔርቍጣ ተሞልቻለሁ፤

በውስጤም ልይዘው አልቻልሁም።

“መንገድ ላይ በሚገኙ ሕፃናት፣

በተሰበሰቡ ወጣቶችም ላይ አፍስሰው፤

ባልም ሚስትም፣

ያረጁና የጃጁም አያመልጡም።

12 በምድሪቱ በሚኖሩት ላይ፣

እጄን በምዘረጋበት ጊዜ፣

ዕርሻቸውና ሚስቶቻቸው ሳይቀሩ፣

ቤቶቻቸው ለሌሎች ይሆናሉ፤”

ይላልእግዚአብሔር።

13 “ከትንሹ እስከ ትልቁ ሰው፣

ሁሉም ለጥቅም የሚስገበገቡ ናቸው፤

ነቢያቱም ካህናቱም ሳይቀሩ፣

ሁሉም ያጭበረብራሉ።

14 የሕዝቤን ቍስል እንደ ቀላል ቈጠሩ፣

እንዲፈወስም ተገቢውን እንክብካቤ አላደረጉለትም፤

ሰላምም ሳይኖር፣

‘ሰላም፣ ሰላም’ ይላሉ።

15 ስለ ጸያፉ ተግባራቸው ዐፍረዋል እንዴ?

ኧረ ጨርሶ ዕፍረት የላቸውም!

ዕፍረት ምን እንደሆነ እንኳ አያውቁም፤

ስለዚህ ከሚወድቁት ጋር ይወድቃሉ፤

በምቀጣቸውም ጊዜ ይዋረዳሉ፤”

ይላልእግዚአብሔር።

16 እግዚአብሔርእንዲህ ይላል፤

“መንታ መንገድ ላይ ቁሙ፣ ተመልከቱም፤

መልካሟን፣ የጥንቷን መንገድ ጠይቁ፤

በእርሷም ላይ ሂዱ።

ለነፍሳችሁ ዕረፍት ታገኛላችሁ፤

እናንተ ግን፣ ‘በእርሷ አንሄድም’ አላችሁ።

17 ጠባቂዎችን አቆምሁላችሁ፤

‘የመለከትንም ድምፅ ስሙ’ አልኋችሁ፤

እናንተ ግን፣ ‘አንሰማም’ አላችሁ።

18 እንግዲህ ሕዝቦች ሆይ ስሙ፤

እናንተም ምስክሮች ምን

እንደሚገጥማቸው አስተውሉ።

19 ምድር ሆይ፤ ስሚ፤

ቃሌን ስላላደመጡ፣

ሕጌንም ስለናቁ፣

በዚህ ሕዝብ ላይ የሐሳባቸውን ውጤት፣

ጥፋትን አመጣባቸዋለሁ።

20 ዕጣን ከሳባ ምድር፣

ጣፋጩ ቅመም ከሩቅ አገር ቢመጣ ምን ይጠቅመኛል?

የሚቃጠል መሥዋዕታችሁን አልቀበልም፤

ሌላውም መሥዋዕታችሁ ደስ አያሰኙኝም፤

21 ስለዚህእግዚአብሔርእንዲህ ይላል፤

በዚህ ሕዝብ ፊት መሰናክልን አስቀምጣለሁ፤

አባቶችና ወንዶች ልጆች በአንድነት ይደናቀፉበታል፤

ጎረቤቶችና ባልንጀሮችም ይጠፋሉ።”

22 እግዚአብሔርእንዲህ ይላል፤

“እነሆ፤ ሰራዊት፣

ከሰሜን ምድር እየመጣ ነው፤

ከምድር ዳርቻም፣

ታላቅ ሕዝብ እየተነሣሣ ነው።

23 ቀስትና ጦር ይዘዋል፤

ጨካኞችና ምሕረት የለሽ ናቸው፤

ፈረሶቻቸውን ሲጋልቡ፤

ድምፃቸው እንደተናወጠ ባሕር ነው፤

የጽዮን ልጅ ሆይ፤ ለሰልፍ የታጠቁ ሆነው፣

ሊወጉሽ ይመጣሉ።”

24 ስለ እነርሱ ወሬ ደርሶናል፤

ክንዶቻችንም ዝለዋል፤

ጭንቀት ይዞናል፤ እንደምታምጥም

ሴት ሆነናል።

25 ጠላት ሰይፍ ታጥቆአል፤

በየቦታውም ሽብር ሞልቶአል፤

ስለዚህ ወደ ውጭ አትውጡ፤

በየመንገዱ አትዘዋወሩ።

26 የሕዝቤ ልጅ ሆይ፤ ማቅ ልበሺ፤

በዐመድም ላይ ተንከባለዪ፤

አንድያ ልጁን እንዳጣ ሰው፣

ምርር ብለሽ አልቅሺ፤

አጥፊው በድንገት፣

በላያችን ይመጣልና።

27 “ብረት እንደሚፈተን፣

የሕዝቤን መንገድ፣

አካሄዳቸውንም እንድትፈትን፣

አንተን ፈታኝ አድርጌሃለሁ።

28 ሁሉም ለማማት የሚዞሩ፣

ድድር ዐመፀኞች፣

ናስና ብረት የሆኑ፣

ምግባረ ብልሹዎች ናቸው።

29 ርሳሱን ለማቅለጥ፣

ወናፉ በብርቱ አናፋ፤

ግን ምን ይሆናል፣ ከንቱ ልፋት ነው፤

ክፉዎች ጠርገው አልወጡምና።

30 እግዚአብሔርንቆአቸዋልና፣

የተናቀ ብር ተብለው ይጠራሉ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *