መዝሙር 141

የክፉዎችን ድሎት ላለመመኘት የቀረበ ጸሎት

1 እግዚአብሔርሆይ፤ ወደ አንተ እጣራለሁ፤ ፈጥነህ ድረስልኝ፤

ወደ አንተ ስጣራም ድምፄን ስማ።

2 ጸሎቴ በፊትህ እንደ ዕጣን ትቈጠርልኝ፤

እጄን ማንሣቴም እንደ ሠርክ መሥዋዕት ትሁን።

3 እግዚአብሔርሆይ፤ ለአፌ ጠባቂ አድርግ፤

የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ።

4 ከዐመፀኞች ጋር፣

በክፉ ሥራ እንዳልተባበር፣

ልቤን ወደ ክፉ አታዘንብል፤

ከድግሳቸውም አልቋደስ።

5 ጻድቅሰው ይቅጣኝ፤ ይህ በጎነት ነው፤

ይገሥጸኝም፤ በራሴ ላይ እንደሚፈስ ዘይት ነው፤

ራሴም ይህን እንቢ አይልም።

ጸሎቴ ግን በክፉዎች ተግባር ላይ ነው፤

6 ሹማምታቸው ከገደል አፋፍ ቍልቍል ይወረወራሉ፣

ቃሌ የምታረካ ናትና፣ ይሰሟታል።

7 ደግሞም፣ “ሰው ምድርን እንደሚያርስና ዐፈሩን እንደሚፈረካክስ፣

እንዲሁ ዐጥንታችን በሲኦልአፋፍ ላይ ተበታተነ” ይላሉ።

8 ጌታእግዚአብሔርሆይ፤ ዐይኖቼ ግን ወደ አንተ ይመለከታሉ፤

መጠጊያዬም አንተ ነህ፤ እንግዲህ ነፍሴን አትተዋት።

9 ከዘረጉብኝ ወጥመድ፣

ከክፉ አድራጊዎችም አሽክላ ጠብቀኝ።

10 እኔ ብቻ በደኅና ሳመልጥ፣

ክፉዎቹ በገዛ ወጥመዳቸው ይውደቁ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *