መዝሙር 61

የግዞተኛ ጸሎት

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች የሚዘመር፤ የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ጩኸቴን ስማ፤

ጸሎቴንም አድምጥ።

2 ልቤ በዛለ ጊዜ፣

ከምድር ዳርቻ ወደ አንተ እጣራለሁ፤

ከእኔ ይልቅ ከፍ ወዳለው ዐለት ምራኝ።

3 አንተ መጠጊያዬ፣

ከጠላትም የምተገንብህ ጽኑ ግንብ ሆነኸኛልና።

4 በድንኳንህ ለዘላለም ልኑር፤

በክንፎችህም ጥላ ልከለል።ሴላ

5 አምላክ ሆይ፤ ስእለቴን ሰምተሃልና፤

ስምህን የሚፈሩትንም ሰዎች ርስት ለእኔ ሰጠህ።

6 የንጉሡን ዕድሜ አርዝምለት፤

ዘመኑንም እስከ ብዙ ትውልድ ጨምርለት፤

7 በእግዚአብሔር ፊት ለዘላለም ይንገሥ፤

ይጠብቁት ዘንድ ምሕረትህንና ታማኝነትህን አዘጋጅለት።

8 ስለዚህ ለስምህ ዘወትር ውዳሴ አቀርባለሁ፤

ስእለቴንም በየጊዜው እፈጽማለሁ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *