መዝሙር 52

የክፉዎች ዕጣ ፈንታ

ለመዘምራን አለቃ፤ ኤዶማዊው ዶይቅ ወደ ሳኦል መጥቶ፣ “ዳዊት ወደ አቢሜሌክ ቤት መጥቶአል” ብሎ በነገረው ጊዜ፤ የዳዊት

ትምህርት

1 ኀያል ሆይ፤ በክፋት ለምን ትኵራራለህ?

አንተ በእግዚአብሔር ዐይን የተናቅህ፣

እንዴትስ ዘወትር ትታበያለህ?

2 አንተ ማታለልን ሥራዬ ብለህ የያዝህ፤

አንደበትህ እንደ ሰላ ምላጭ፣

ጥፋትን ያውጠነጥናል።

3 ከበጎ ነገር ይልቅ ክፋትን፣

እውነትን ከመናገር ይልቅ ሐሰትን ወደድህ።ሴላ

4 አንተ አታላይ አንደበት ሆይ፤

ጐጂ ቃላትን ሁሉ ወደድህ!

5 እግዚአብሔር ግን ለዘላለም

ያንኰታኵትሃል፤

ይነጥቅሃል፤ ከድንኳንህም መንጥቆ ያወጣሃል፤

ከሕያዋንም ምድር ይነቅልሃል።ሴላ

6 ጻድቃን ይህን ዐይተው ይፈራሉ፤

እንዲህ እያሉም ይሥቁበታል፤

7 “እግዚአብሔርን መጠጊያ ያላደረገ፣

ነገር ግን በሀብቱ ብዛት የተመካ፣

በክፋቱም የበረታ፣

ያ ሰው እነሆ!”

8 እኔ ግን በእግዚአብሔር ቤት፣

እንደለመለመ የወይራ ዛፍ ነኝ፤

ከዘላለም እስከ ዘላለም፣

በእግዚአብሔር ምሕረት እታመናለሁ።

9 ስላደረግኸው ነገር ለዘላለም አመሰግንሃለሁ፤

ስምህ መልካም ነውና ስምህን ተስፋ አደርጋለሁ፤

በቅዱሳንም መካከል አመሰግንሃለሁ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *