የፈጣሪ ግርማ በፍጥረቱ ላይ
ለመዘምራን አለቃ፣ በዋሽንት የሚዜም፤ የዳዊት መዝሙር
1 እግዚአብሔርአምላካችን ሆይ፤
ስምህ በምድር ሁሉ ላይ ምንኛ ግርማዊ ነው!
ክብርህ ከሰማያት በላይ፣
ከፍ ከፍ ብሎአል።
2 ከልጆችና ጡት ከሚጠቡ ሕፃናት አፍ፣
ምስጋናንአዘጋጀህ፤
ከጠላትህ የተነሣ፣
ባላንጣንና ቂመኛን ጸጥ ታሰኝ ዘንድ።
3 የጣቶችህን ሥራ፣
ሰማያትህን ስመለከት፣
በስፍራቸው ያኖርሃቸውን፣
ጨረቃንና ከዋክብትን ሳይ፣
4 በሐሳብህ ስፍራ ትሰጠው ዘንድ ሰው ምንድን ነው?
ትጠነቀቅለትም ዘንድ የሰው ልጅ ምንድን ነው?
5 ከመላእክት በጥቂት አሳነስኸው፤
የክብርንና የሞገስን ዘውድ አቀዳጀኸው።
6 በእጆችህ ሥራ ላይ ሾምኸው፤
ሁሉንም ከእግሩ በታች አስገዛህለት፤
7 በጎችንና ላሞችን ሁሉ፣
የዱር አራዊትንም፣
8 የሰማይ ወፎችንና፣
የባሕር ዓሦችን፣
በባሕር ውስጥ የሚርመሰመሱትንም ሁሉ አስገዛህለት።
9 እግዚአብሔርአምላካችን ሆይ፤
ስምህ በምድር ሁሉ ላይ ምንኛ ግርማዊ ነው!