ዘፀአት 15

የሙሴና የማርያም መዝሙር

1 ከዚያም ሙሴና እስራኤላውያን ይህን መዝሙርለእግዚአብሔር(ያህዌ)ዘመሩ፤

“ከፍ ከፍ ብሎ ከብሮአልና፣

ለእግዚአብሔር(ያህዌ)እዘምራለሁ፤

ፈረሱንና ፈረሰኛውን፣

በባሕር ውስጥ ጥሎአልና።

2 ለእግዚአብሔር(ያህዌ)ብርታቴና ዝማሬዬ ነው፤

ድነቴም ሆነልኝ፤

እርሱ አምላኬ ነው፤ አመሰግነዋለሁ፤

የአባቴ አምላክ(ኤሎሂም)ነው፤ እኔም ከፍ ከፍ አደርገዋለሁ።

3 ለእግዚአብሔር(ያህዌ)ተዋጊ ነው፤

ስሙምእግዚአብሔር(ያህዌ)ነው።

4 የፈርዖንን ሠረገሎችና ሰራዊት፣

ባሕር ውስጥ ጣላቸው፤

ምርጥ የሆኑት የፈርዖን ሹማምት፣

ቀይ ባሕር ውስጥ ሰጠሙ።

5 ቀላያትንም ለበሱ፤

እንደ ድንጋይ ወደ ጥልቁ ወረዱ።

6 “አቤቱእግዚአብሔር(ያህዌ)ሆይ፤

ቀኝ እጅህ በግርማ ከበረ፤

አቤቱእግዚአብሔር(ያህዌ)ሆይ፤

ቀኝ እጅህ ጠላትን አደቀቀ።

7 በግርማህ ታላቅነት፣

የተቃወሙህን ጣልኻቸው፤

ቍጣህን ሰደድህ፤

እንደ ገለባም በላቸው።

8 በአፍንጫህ እስትንፋስ፣

ውሆች ተቈለሉ፤

ፈሳሾችም እንደ ግድግዳ ቆሙ፤

የጥልቁ ውሃ ባሕሩ ውስጥ ረጋ።

9 “ጠላት፣ ‘አሳድዳቸዋለሁ፤

እማርካቸዋለሁ፤

ምርኮን እካፈላለሁ፤

ነፍሴ በእነርሱ ትጠግባለች፤

ሰይፌን እመዛለሁ፤

እጄም ትደመስሳቸዋለች አለ።

10 አንተ ግን እስትንፋስህን አነፈስህ፤

ባሕርም ከደናቸው፤

በኀያላን ውሆች፣

እንደ ብረት ሰጠሙ።

11 “አቤቱእግዚአብሔር(ያህዌ)ሆይ፤

ከአማልክት መካከል፣ እንደ አንተ ማን አለ?

በቅድስናው የከበረ፣

በክብሩ የሚያስፈራ፣

ድንቆችን የሚያደርግ፣

እንደ አንተ ማን አለ?

12 ቀኝ እጅህን ዘረጋህ፤

ምድርም ዋጠቻቸው።

13 ‘በማይለወጠው ፍቅርህ፣

የተቤዥሃቸው ሕዝብህን ትመራለህ፤

እነርሱን በብርታትህ፣

ወደ ቅዱስ ማደሪያህ ትመራቸዋለህ።

14 አሕዛብ ይሰማሉ፤ ይንቀጠቀጡማል፤

የፍልስጥኤምን ሕዝብ ሥቃይ ይይዛቸዋል።

15 የኤዶምም አለቆች ይርዳሉ፤

የሞአብ አለቆች በእንቅጥቃጤ ይያዛሉ፤

የከነዓን ሕዝብ ይቀልጣሉ።

16 አቤቱእግዚአብሔር(ያህዌ)ሆይ፤ ሕዝብህ

እስከሚያልፉ ድረስ፣

የተቤዠኻቸው ሕዝብህ እስኪያልፉ ድረስ፣

ድንጋጤና ሽብር በእነርሱ ላይ ይመጣል፤

በክንድህ ብርታት፣

እንደ ድንጋይ የማይንቀሳቀሱ ይሆናሉ።

17 እግዚአብሔር(ያህዌ)ሆይ፤ ማደሪያህ

እንዲሆን በሠራኸው ስፍራ፣

ጌታ(አዶናይ)ሆይ፤ እጆችህ በሠሩት መቅደስ፣

በርስትህ ተራራ ላይ፣ ታመጣቸዋለህ፤ ትተክላቸዋለህም።

18 እግዚአብሔር(ያህዌ)፣

ከዘላለም እስከ ዘላለም ይነግሣል።”

19 የፈርዖን ፈረሶች፣ ሠረገሎቹናፈረሰኞቹ ወደ ባሕሩ በገቡ ጊዜእግዚአብሔር(ያህዌ)የባሕሩን ውሃ በላያቸው ላይ መለሰባቸው፤ እስራኤላውያን ግን በባሕሩ ውስጥ በደረቅ ምድር ተሻገሩ።

20 ከዚያም የአሮን እኅት ነቢይቱ ማርያም ከበሮዋን አንሥታ ያዘች፤ የቀሩትም ሴቶች ሁሉ ከበሮ ይዘው እያሸበሸቡ ተከተሏት።

21 ማርያምም፣

“ፈረሱንና ፈረሰኛውን፣

በባሕር ውስጥ ጥሎአል፤እግዚአብሔር(ያህዌ)ዘምሩ፤

እጅግ ከፍ ከፍ ብሎአልና”

እያለች ዘመረችላቸው።

የማራና የኤሊም ውሃ

22 ከዚያም ሙሴ እስራኤልን ከቀይ ባሕር እየመራቸው ወደ ሱር ምድረ በዳ ሄዱ፤ ለሦስት ቀናት ውሃ ሳያገኙም በምድረ በዳ ተጓዙ።

23 ማራ በደረሱ ጊዜ ውሃው መራራ ስለ ነበር ሊጠጡት አልቻሉም፤ ቦታው ማራ ተብሎ የተጠራውም ከዚህ የተነሣ ነው።

24 ሕዝቡም በሙሴ ላይ በማጉረምረም፣ “ምን እንጠጣ?” አሉ።

25 ከዚያም ሙሴ ወደእግዚአብሔር(ያህዌ)ጮኸ፤እግዚአብሔር(ያህዌ)አንዲት ዛፍ አሳየው፤ ዕንጨቷንም ወደ ውሃው ጣላት፤ ውሃውም ጣፋጭ ሆነ።

በዚያምእግዚአብሔር(ያህዌ)ሕግና ሥርዐት አበጀላቸው፤ በዚያም ሥፍራ ፈተናቸው።

26 እርሱም አለ፤ “የአምላካችሁንእግዚአብሔር(ያህዌ)ድምፅ በጥንቃቄ ብትሰሙ፣ በፊቱም ትክክል የሆነውን ብትፈጽሙ፣ ትእዛዛቱን ልብ ብትሉና ሥርዐቱንም ሁሉ ብትጠብቁ፣ በግብፃውያን ላይ ያመጣሁባቸውን ማንኛውንም ዐይነት በሽታ በእናንተ ላይ አላመጣም፤ ፈዋሻችሁ እኔእግዚአብሔር(ያህዌ)ነኝና።”

27 ከዚያም ዐሥራ ሁለት ምንጮችና ሰባ የዘንባባ ዛፎች ወዳሉበት ወደ ኤሊም መጡ፤ እነርሱም በውሃው አጠገብ በዚያ ሰፈሩ።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *