የእግዚአብሔር ፍቅር ለእስራኤል
1 “እስራኤል ገና ሕፃን ሳለ ወደድሁት፤
ልጄንም ከግብፅ ጠራሁት።
2 እስራኤል ግን አብዝቼ በጠራኋቸውቍጥር፣
አብዝተው ከእኔራቁ፤
ለበኣል አማልክት ሠዉ፤
ለምስሎችም ዐጠኑ።
3 ኤፍሬምን እጁን ይዤ፣
እንዲራመድ ያስተማርሁት እኔ ነበርሁ፤
ነገር ግን የፈወስኋቸው እኔ እንደሆንሁ፣
እነርሱ አላስተዋሉም።
4 በሰው የርኅራኄ ገመድ፣
በፍቅርም ሰንሰለት ሳብኋቸው፤
ቀንበሩን ከጫንቃቸው ላይ አነሣሁላቸው፤
ዝቅ ብዬም መገብኋቸው።
5 “ታዲያ ንስሓ መግባትን እምቢ በማለታቸው፣
ወደ ግብፅ አይመለሱምን?
አሦርስ አይገዛቸውምን?
6 በከተሞቻቸው ላይ ሰይፍ ይመዘዛል፤
የበሮቻቸውን መወርወሪያ ይቈርጣል፤
ስለ ክፉ ዕቅዳቸውም ይደመስሳቸዋል።
7 ሕዝቤ ከእኔ ዘወር ማለትን መረጡ፤
ወደ ልዑል ቢጣሩም፣
በምንም ዐይነት አያከብራቸውም።
8 “ኤፍሬም ሆይ፤ እንዴት እጥልሃለሁ?
እስራኤል ሆይ፤ እንዴትስ አሳልፌ እሰጥሃለሁ?
እንዴት እንደ አዳማ አደርግሃለሁ?
እንዴትስ እንደ ሲባዮ እፈጽምብሃለሁ?
ልቤ በውስጤ ተናወጠ፤
ምሕረቴም ሁሉ ተነሣሥቶአል።
9 የቊጣዬን መቅሠፍት አላመጣም፤
ተመልሼም ኤፍሬምን አላጠፋም፤
እኔ በመካከላችሁ ያለሁ ቅዱስ አምላክ ነኝ እንጂ፣
ሰው አይደለሁምና፣
በቊጣ አልመጣም።
10 እግዚአብሔርንይከተላሉ፤
እርሱም እንደ አንበሳ ያገሣል፤
እርሱ ሲያገሣ፣
ልጆቹ እየተንቀጠቀጡ ከምዕራብ ይመጣሉ።
11 እንደ ወፍ ከግብፅ፣
እንደ ርግብ ከአሦር፣
እየበረሩ ይመጣሉ።
እኔም በቤታቸው አኖራቸዋለሁ፤”
ይላልእግዚአብሔር።
የእስራኤል ኀጢአት
12 ኤፍሬም በሐሰት፣
የእስራኤልም ቤት በተንኰል ከበበኝ፤
ይሁዳ ለአምላክ የማይገዛ፣
የታመነውን ቅዱሱን የሚቃወም ነው።