መዝሙር 75

ለመለኮታዊው ዳኛ የቀረበ ዝማሬ

ለመዘምራን አለቃ፤ “አታጥፋ” በሚለው ቅኝት የሚዜም፤ የአሳፍ መዝሙር ማሕሌት

1 አምላክ ሆይ፤ ምስጋና እናቀርብልሃለን፤

ስምህ ቅርብ ነውና ምስጋና እናቀርብልሃለን፤

ሰዎችም ስለ ድንቅ ሥራህ ይናገራሉ።

2 አንተም እንዲህ አልህ፤ “ለይቼ በወሰንኋት ሰዓት፣

በቅን የምፈርድ እኔ ነኝ።

3 ምድርና ሕዝቦቿ ሁሉ በሚናወጡበት ጊዜ፣

ምሰሶቿን አጽንቼ የምይዝ እኔ ነኝ።ሴላ

4 እብሪተኛውን፣ ‘አትደንፋ’፤

ክፉውንም ‘ቀንድህን ከፍ አታድርግ እለዋለሁ፤

5 ቀንድህን ወደ ሰማይ አታንሣ፤

ዐንገትህንም መዝዘህ አትናገር።’ ”

6 ክብር ከምሥራቅ ወይም ከምዕራብ፣

ወይም ከምድረ በዳ አይመጣምና፤

7 ነገር ግን የሚፈርድ እግዚአብሔር ነው፤

እርሱ አንዱን ዝቅ፣ ሌላውን ከፍ ያደርጋል።

8 በእግዚአብሔርእጅ ጽዋ አለ፤

በሚገባ የተቀመመና ዐረፋ የሚወጣው የወይን ጠጅ ሞልቶበታል፤

ይህን ከውስጡ ወደ ውጭ ገለበጠው፤

የምድር ዐመፀኞችም አተላው ሳይቀር ይጨልጡታል።

9 እኔ ግን ይህን ለዘላለም ዐውጃለሁ፤

ለያዕቆብም አምላክ ዝማሬ አቀርባለሁ።

10 የክፉዎችን ሁሉ ቀንድ እሰብራለሁ፤

የጻድቃን ቀንድ ግን ከፍ ከፍ ይላል።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *